የመስቀል ደመራ በዓል ለመጀመሪያ ጊዜ በድምቀት ተከበረ

የመስቀል ደመራ በዓል ለመጀመሪያ ጊዜ በድምቀት ተከበረ

በፊንላንድ ሄልሲንኪ ከተማ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተክርስቲያን አደባባይ. /ሜዳ / ላይ በተካሄደው የደመራ ሥነ ሥርዓት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ መጋቤ ብሉይ ቀሲስ ለማ በሱፈቃድ፣ የሄልሲንኪ ከተማ ምክትል ከንቲባ ሪትቫ ቪልያነን ፣ የደብሩ ዲያቆናት ፣ የሄልሲንኪ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ካህናት ዲያቆናት እና ምእመናን ፣ ጥንግ ድርብ የለበሱ የደብሩ መዘምራን፣ ሕጻናት፣ ከሄልሲንኪና ከአጎራባች ከተሞች የመጡ ምእመናን፣ የባህል እና የሌሎች ተቋማት ሓላፊዋች ፣ጋዜጠኞች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት መስከረም 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ከ 17፡30 – 20፡30 በተካሄደ የመስቀል ደመራ ሥነ ሥርዓት በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል።

ሥነ ሥርዓቱ ከመጀመሩ ቀደም ብሎ የበዓሉ ልዩ መገለጫ የሆነው ደመራ በተዘጋጀው ቦታ ላይ ተደምሮ የቆመ ሲሆን ፣ በመቀጠልም በካህናቱና በዲያቆናቱ መሪነት ዕለቱን የሚያዘክር ስብሐተ እግዚአብሔር ደርሷል፡፡ ስብሐተ እግዚአብሔር ከደረሰ በኋላም ፣ የደብሩ መዘምራን በመጀመሪያ ”ዝንቱ መስቀል ቤዛነ መድኃኒትነ” የሚለውን ያሬዳዊ ወረብ ያቀረቡ ሲሆን ፣ በመቀጠልም ለበዓሉ ያዘጋጇቸውን ሌሎች መዝሙራት አቅርበዋል፡፡ የደብሩ አዳጊ ሕጻናትም በተመደበላቸው ሰዓት መዝሙራትን ያቀረቡ ሲሆን፣ በበዓሉ ላይ የተገኙ የሀገሪቱን ነዋሪዎች ታሳቢ በማድረግ ካቀረቧችው መዝሙራት ውስጥ የተወሰኑትን መዝሙራት በፊላንድኛ ቋንቋ ዘምረዋል። በዓሉንም በማስመልከት ሰለ መስቀሉ በፊላንድኛ ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ በመቀባበል አቅርበዋል ፡፡dsc_0974

ለበዓሉ በተያዘው መርሃ ግብር መሠረት ቀጥሎ የቀረበው፣ መስቀልን የሚመለከት አጠር ያለ ትምህርተ ወንጌል ሲሆን፣ የቅዱስ ጳውሎስን ”የመስቀሉ ነገር ለሚጠፉት ሞኘነት ነው” የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ በመጋቤ ብሉይ ቀሲስ ለማ በሱፈቃድ የደብሩ አስተዳዳሪ ተሰጥቷል፡፡ የደመራው ችቦ ከመለኮሱ ቀደም ብሎ በሊቃውንቱ መሪነት ያሬዳዊ ዜማዎች የቀረቡ ሲሆን ፣ምእመኑም ካህናቱን በማጀብና ደመራውን መዞር በኅብረት በዝማሬ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡

በበዓሉ ላይ የተገኙት የሄልሲንኪ ከተማ ምክትል ከንቲባ ሪትቫ በበዓሉ ላይ በመገኝታቸው ከፍተኛ የሆነ የደስታና የመደነቅ ሰሜት እንደ ተሰማቸው በሰጡት አስተያየት ገልጸዋል። አያይዘውም እንደዚህ አይነቱ ታላቅ በዓል በፊላንድ ሄልሲንኪ መከበሩ ብዙኃንነትን እንዲጨምር ያደርጋል ብለዋል። በተጨማሪም በፊንላንድ የሚኖረው የኢትዮጵያ ማህበረሰብ በጣም ዝቅተኛ የሥራ አጥ ቁጥር ያለው ታታሪ ማሕበረሰብ እንደሆነ እና ከፊላንድ ህዝብም ጋር ተስማምቶ እየኖረ መሆኑን ገልጸዋል።

dsc_0102ደመራውን ለመለኮስ የተያዘው ሰዓት ሲደርስ፣ በካህናቱና በተጋባዥ የክብር እንግዶች አማካኝነት ደመራው የተለኮሰ ሲሆን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑም ደመራውን ከበው በዝማሬና በእልልታ ምስጋናቸውን በማቅረብ በዓሉን አድምቀውት አምሽተዋል፡፡ በመጨረሻም የማሳረጊያ ጸሎት ደርሶ የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

በበዓሉ የተኙት በሄልሲንኪና አጎራባች ከተሞች የሚኖሩ ምእመናን በባሕላዊ ልብስ ደምቀው፣ ደመራው ከበራም በኋላ ጧፍ በማብራት በበዓሉ ላይ ልዩ ገጽታ ፈጥረዋል፡፡የተባበሩት መንግስታት የሳይንስ የትምህርትና ባህል ማዕከል/UNESCO/ የኢትዮጵያን የመስቀል በዓል አከባበር በዓለም ቅርስነት መመዝገቡ የሚታወስ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ካስመዘገበቻቸው ዘጠኝ የሚዳሰሱ ዓለም አቀፍ ቅርሶች በተጨማሪ የመስቀል ክብረ በዓል አሥረኛውና የመጀመሪያው የማይዳሰስ/ የማይጨበጥ ቅርስ በመሆን የተመዘገበ በዓል መሆኑ የሚታወስ ነው።

የመስቀሉ በረከት ከሁላችን ጋራ ይሁን።

የደመራ በዓል አከባበር 2016

share

Comments

  1. Feven Tigistu-Sahle : September 30, 2016 at 11:50 am

    አሜን ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ በዓለ ጥመቀቱን እንዲህ ባማረ ሁኔታ ለማክበር በመታደላችን በጣም ደስ ብሎኛል። ወስብሃተ ለእግዚአብሔር!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *