ልደተ ክርስቶስ /የገና በዓል/ – ለሕጻናት

ልደተ ክርስቶስ /የገና በዓል/ - ለሕጻናት

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? ዛሬ ስለጌታችን አምላካችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት /ገና በዓል/ እንነግራችኋለን፡፡ በደንብ ተከታተሉን፡፡ እሺ?

ልጆች በአንድ ወቅት እንዲህ ሆነ፡፡ አውግስጦስ ቄሳር የተባለ ንጉሥ ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ አዘዘ፡፡ በትእዛዙ መሠረትም ሰው ሁሉ ሊቆጠር ወደየትውልድ ከተማው ሄደ፡፡ ዮሴፍና እመቤታችንም ሊቆጠሩ ከናዝሬት ወደ ትውልድ ሥፍራቸው ወደ ቤተልሔም ሄዱ፡፡ በቤተልሔም ሳሉም እመቤታችን የምትወልድበት ቀን ደረሰ፡፡ በዚያ ሥፍራም ብዙ እንግዳ ስለነበር እነ ዮሴፍ የሚያርፉበት ቦታ አላገኙም ነበር፡፡ ማደርያም ስላልነበራቸው በከብቶች ማደርያ በበረት ውስጥ እመቤታችን ልጅዋን ወለደችው፡፡
በጨርቅ ጠቅልላ እዛው በበረት ውስጥ አስተኛችው፤ በዚያ ሀገር ይኖሩ የነበሩ እረኞችም ሌሊት ከብቶቻቸውን ይጠብቁ ነበር፤ የእግዚአብሔር መልአክም በእረኞቹ አጠገብ ቆመ፤ የእግዚአብሔርም ብርሃን በዙሪያቸው በራ፤ በጣምም ፈሩ፡፡ መልአኩም እንዲህ አላቸው ‹‹እነሆ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን ታላቅ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ‹‹እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት የሆነ ተወልዶላችኋል፡፡ ይኸውም ጌታ እና እግዚአብሔር የሆነ መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እናንተም ባገኛችሁት ጊዜ ምልክቱ እንዲህ ነው፡፡ ሕፃን በጨርቅ ተጠቅልሎ በበረት ውስጥ ተኝቶ ታገኙታላችሁ ድንገትም ከዚያ መልአክ ጋር ብዙ የሰማይ መላእክት እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ እነዚህ እረኞች እርስ በርሳቸው ‹እስከ ቤተልሔም እንሂድ እግዚአብሔርም የገለጠልንን ይህን ነገር እንወቅ አሉ፡፡ ፈጥነውም ሄዱ፡፡ ማርያምንና ዮሴፍን አገኙአቸው፡፡ ሕፃኑንም በበረት ውስጥ አገኙት፡፡ በአዩትም ጊዜ የነገሩአቸውን ሰምተው በጣም ተደነቁ፡፡ እረኞቹም እንደነገሩአቸው ባዩትና በሰሙት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ‹‹በሰማይ ለእግዚአብሔር ክብር ይሁን በምድርም ለሰው ልጆች በጎፈቃድ ሆነ›› ብለው እያመሰገኑና እያከበሩ ወደመጡበት ተመለሱ፡፡ አያችሁ ልጆች እነዚህ ክርስቶስን ሊያዩ የመጡ ሰዎች ደስተኞች ነበሩ፤ ስለዚህ ልጆች እኛም በቤተ ክርስቲያን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት በደስታ ልናከብር ይገባናል፡፡ ከመላእክት ጋር ሆነንም ‹‹በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን›› እያልን እንዘምር፡፡ እንግዲህ ልጆች መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ እሺ፡፡
ምንጭ  www.eotcmk.org
share

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *